Deuteronomy 34

የሙሴ መሞት

1ሙሴ ከሞዓብ ሜዳ ተነሥቶ ለኢያሪኮ ትይዩ ወደ ሆነው ፈስጋ ጫፍ፣ ወደ ናባው ተራራ ወጣ። በዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) ምድሪቱን ሁሉ አሳየው፤ ይኸውም ከገለዓድ እስከ ዳን፣ 2ንፍታሌምን ሁሉ፣ የኤፍሬምንና የምናሴን ግዛት፣ እስከ ምዕራብ ባሕር
ይኸውም የሜዲትራንያን ባሕር ነው።
ድረስ ያለውን የይሁዳን ምድር ሁሉ፣
3ኔጌብንና የዘንባባ ከተማ ከሆነችው ከኢያሪኮ ሸለቆ እስከ ዞዓር ያለውን ምድር ሁሉ ነው። 4ከዚያም በኋላ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን “ለአብርሃም፣ ለይስሐቅና ለያዕቆብ፣ ‘ለዘሮቻችሁ እሰጣለሁ’ ብዬ በመሐላ ቃል የገባሁላቸው ምድር ይህች ናት። በዐይንህ እንድታያት አድርጌአለሁ፤ ነገር ግን ወደዚያ አትሻገርም” አለው።

5 እግዚአብሔር (ያህዌ) እንደ ተናገረው የእግዚአብሔር (ያህዌ) አገልጋይ ሙሴ በሞዓብ ምድር ሞተ። 6በሞዓብ ምድር በቤተ ፌጎር ፊት ለፊት ባለው ሸለቆ ቀበረው
ወይም፣ ተቀበረ ብሎ መተርጐም ይቻላል።
፤ ይሁን እንጂ መቃብሩ የት እንደ ሆነ እስከ ዛሬ ማንም አያውቅም።
7ሙሴ በሞተ ጊዜ ዕድሜው መቶ ሃያ ዓመት ነበር፤ ሆኖም ዐይኑ አልፈዘዘም፤ ጕልበቱም አልደከመም። 8የልቅሶውና የሐዘኑ ጊዜ እስኪያበቃ ድረስ፣ እስራኤላውያን በሞዓብ ሜዳ ሠላሳ ቀን አለቀሱለት።

9ሙሴ እጆቹን ጭኖበት ነበርና፣ የነዌ ልጅ ኢያሱ በጥበብ መንፈስ ተሞላ። ስለዚህ እስራኤላውያን አደመጡት፤ እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን አዝዞት የነበረውንም ሁሉ አደረጉ።

10 እግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ለፊት ያወቀው እንደ ሙሴ ያለ ነቢይ ከዚያ ወዲህ በእስራኤል አልተነሣም። 11እግዚአብሔር (ያህዌ) ልኮት፣ እነዚያን ታምራዊ ምልክቶችና ድንቆች ሁሉ በግብፅ በፈርዖን፣ በሹማምቱና በምድሪቱ ሁሉ ላይ እንዲያደርግ የላከውን ያደረገ ማንም ሰው አልነበረም። 12ሙሴ በእስራኤል ሁሉ ፊት ያሳየውን ታላቅ ኀይል ያሳየ ወይም ያደረገውን አስፈሪ ተግባር የፈጸመ ማንም ሰው የለም።

Copyright information for AmhNASV